Saturday, April 30, 2016

እንኳን ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሳኤ በዓል በሰላም አደረሰን፥ አደረሳችሁ!

እንኳን ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሳኤ በዓል በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!


በዐማርኛችን ፋሲካ የምንለው ቃል በዕብራጥስጥ አፍ፥ አቻ ቃሉ פֶּסַח 6453 pecach peh'-sakh፣ ፔሳኽ” የሚል ሲሆን ትርጓሜውም “አለፈ፣ ተሻገር” እንደማለት ነው። ይህ ፋሲካ የሚለው ቃል የዐማርኛ ቃል ትርጓሜው፥ ፍሥሃ፣ ሐሴት፣ መሻገር፣ ማለፍ ማለት ነው፡፡

 ከዚህ በመነሳት በዓለ ፋሲካ የምናከብረው፥ በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ሞትን ተሻግረን፣ ባርነትን አምልጠን፣ የእግዚአብሔር ልጆች የሆነበትን የትንሳኤውን ድል በማስብ ነው፡፡ ይህ በዓል በመጽሐፍ ቅዱሳችን ላይ በዘጽአት መጽሐፍ፥ በአሥራ ሁለተኛው ምዕራፍ ላይ ከሰፈረው ታሪክ ጥላነቱን ይዞ የሚጀምር ነው፥

·        እኔም በዚያች ሌሊት በግብፅ አገር አልፋለሁ፥ በግብፅም አገር ከሰው እስከ እንስሳ ድረስ በኵርን ሁሉ እገድላለሁ በግብፅም አማልክት ሁሉ ላይ እፈርድባቸዋለሁ እኔ እግዚአብሔር ነኝ። ደሙም ባላችሁበት ቤቶች ምልክት ይሆንላችኋል ደሙንም ባየሁ ጊዜ ከእናንተ አልፋለሁ እኔም የግብፅን አገር በመታሁ ጊዜ መቅሰፍቱ ለጥፋት አይመጣባችሁም። ዘጽ 12፥12-13፡፡

ጌታ እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ባዘዛቸው መሰረት፥ ከአንድ ዓመት የማይበልጠውን የፍየል ወይም የበግ ጠቦት መስዋዕት አርደው፥ የቤታቸውን መቃንና ጉበን ከመስዋዕቱ ደም ቀብተው፥ ያልፍ ከነበረው የእግዚአብሔር መቅሰፍት አምልጠዋል፡፡ የእግዚአብሔር መቅሰፍት በመጣ ጊዜ፥ የደሙ ምልክት የሌለውን ቤት እየገባ በኩረ ግብጽን በሞት ሲቀጣ፥ እስራኤላውያንን ግን ይህ ታላቅ መቅሰፈት ቤታቸውን እንኳ ሳያንኳኳ፥ በመቃኑና በጉበኑ ላይ ከተቀባው የመስዋዕቱ ደም የተነሳ ያልፍ ነበር፡፡ ይህም ፋሲካ ተባለ።

ይህ ሁሉ ለአዲስ ኪዳኑ ፋሲካ፥ ጥላ ሆኖ የቆየ ነበር፡፡ አካላዊው ፋሲካ ጌታችን ኢየሱስ መሆኑን የአዲስ ኪዳን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፥

·        «እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ። ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና» 1ኛ ቆሮ 5፥7።  

በአዲስ ኪዳን ደግሞ ከሞት የሚያስመልጥ የደሙ ምልክት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ይህ መስዋዕት ሰው ያላዘጋጀውና በራሱ በእግዚአብሔር ለሰው ልጆች ከሞት የመዳን ዋስትና የተዘጋጀ ሲሆን እንደ ብሉይ ኪዳኑ መስዋዕት በየጊዜው ደም በማፍሰስ ከሞት ለማዳን ያልቀረበ ነገር ግን አንዴ ተፈጽሞ ለዘለዓለሙ የሚያገለግል ዘላለማዊ የመስዋዕት ደም ነው። ለዛም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፥ የቀደመው ማንነታችንን ትተን፥ የዐመጻና የኃጢአት እርሾችንን በንስሐ አስወግደን፥ በእምነት የምንቀበለው አዲሱ ፋሲካ ክርስቶስ እንደሆነ የጻፈልን። ይህም ብቻ አይደለም፥ እስራኤላውያንን የፍየል መስዋዕቱ ደም ያልፍ ከነበረው ከቁጣው መቅሰፍት እንዳሻገራቸው ሁሉ፥ የአዲስ ኪዳኑ ነውርና ነቀፋ የሌለው የጌታችን የኢየሱስ ደም ደግሞ ከዘላለም ሞት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔር ልጅ የመሆንን ጸጋና ርስቱንም ጨምሮ አውርሶናል፥

·        “ስለዚህም የፊተኛው ኪዳን ሲጸና ሕግን የተላለፉትን የሚቤዥ ሞት ስለ ሆነ፥ የተጠሩት የዘላለምን ርስት የተስፋ ቃል እንዲቀበሉ እርሱ የአዲስ ኪዳን መካከለኛ ነው።” ዕብ 9፥15፡፡

አሜን!! መልካም የትንሳኤ በዓል ይሁንል!!

2 comments: